ጥቅስ

ጌታዬ
እግዚአብሔር ሆይ
እስከዚህ ያደረስኸኝ
እኔ ማን ነኝ ?
ቤቴስ ምንድር ነው?
2 ሳሙ 7፥18

Wednesday 31 July 2013

ትምህርተ ጋብቻ ክፍል ፫ (3)

ከ መልአከ ሰላም ቀሲስ ደጀኔ ሺፈራው ብሎግ የተወሰደ
፩፦ መጠናናት፤
            ምንም እንኳን የሰው ልጅ ተጠንቶ የማያልቅ ሳይንስ ቢሆንም ፦ ወደ ትዳር ዓለም ከመግባት በፊት ፦እንደ ሰው፥ በሰው አቅም መጠናናት እንደሚያስፈልግ ለማንም ግልጥ ነው። ይኸውም በሰከነ ልቡና ፥ በተረጋጋ መንፈስ ሊሆን ይገባል። በትውውቅ ሰሞን የተሸፈነ ብዙ ነገር ፥ በሂደት ቀስ እያለ ብቅ ማለቱ ስለማይቀር ጊዜ መስጠት ያስፈልጋል። ሰውን የምናጠናው ድካም የሌለበት ፍጹም የሆነ ሰው ለማግኘት አይደለም። ምክንያቱም እኛም ፍጹም አይደለንምና ነው ፥ አንድም በዓለመ ሥጋ ፍጹም ሰው አይገኝምና ነው። በመሆኑም፦ በእኛ ዘንድ ድካም እንዳለ ሁሉ ፦ በሌላም በኲል ድካም ሊኖር እንደሚችል አምነን ኅሊናችንን ልናዘጋጀው ይገባል። ከዚ ህ በኋላ ድካሙን ፦ በአራት ደረጃ ከፍለን ልናየው እንችላለን። ፩ኛ፦ በቶሎ የሚወገድ ድካም ፤ ፪ኛ ፦ በሂደት የሚወገድ ድካም፤ ፫ኛ፦ ልንሸከመው የሚገባን ድካም፤ ፬ኛ ፦ የማይወገድ ድካም፤
፩፥፩፦ በቶሎ የሚወገድ ድካም፤
            የሰው ልጅ በትምህርት ፥ በምክርና በተግሣጽ ፦ ከጥፋቱ ሊመለስ ፥ ከድካሙም ሊበረታ ይችላል። ስለሆነም ያሉትን ደካማ ጐኖች ዘርዝሮ በማውጣት ፦ እርስ በርስ መነጋገር ፥ መማማር ያስፈልጋል። ከአቅም በላይ የሆነውን ደግሞ ወደ ካህኑ በማምጣት ማስ መከር ይገባል። እንዲህ ዓይነቱ ድካም ፦ ከእውቀት ማነስ፥ ከመካሪ ማጣት ፥ አርአያ የሚሆን ሰው ካለማግኘት በመሆኑ በቶሎ ይወ ገዳል። ጠቢቡ ሰሎሞን፦ «ምክር በሰው ልቡና እንደ ጥልቅ ውኃ ነው፤ አእምሮ ያለው ሰው ግን ይቀዳዋል።» እንዳለ፦ አእምሮ ያላቸው የሚያስተውሉ ሰዎች ይስተካከሉበታል። ምሳ ፳፥፭። «ተግሣጽን የሚወድድ ዕውቀትን ይወድዳል፤» እንዲል፦ በሁሉ ይገሠጻሉ። ምሳ ፲፪፥፩። «የተማረ ልጅ ብልህ ይሆናል፤» እንዲል፦ ልባሞች ፥ አስተዋዮች እየሆኑ ይሄዳሉ። ምሳ ፲፥፭። ይህም ከምድራዊ ሀብት የሚበልጥ ሀብት ነው። ምክንያቱም « ከብር ይልቅ ትምህርትን ፥ ከተፈተነ ወርቅም ይልቅ ዕውቀትን ተቀበሉ ፤ » ይላልና። ምሳ ፰፥፲። «ትምህርትና ተግሣጽም የሕይወት መንገድ ነውና፤» የሚልም አለ። ምሳ ፮፥፳፫።

ትምህርተ ጋብቻ፡- ክፍል ፪ (2)


 ከ መልአከ ሰላም ቀሲስ ደጀኔ ሺፈራው ብሎግ የተወሰደ



፩፡- የትዳር ጓደኛን ማን ይምረጥልን?

          የትዳር ጓደኛ በሰው ልጅ ሕይወት ውስጥ መሠረታዊ ጉዳይ ነው። ባለጸጋ ፥ወይም ባለሥልጣን፥ ወይም ቆንጆ፥ ወይም ጤነኛ፥ ስለሆኑ ብቻ የሚሹት አይደለም። ደሀ፥ ወይም ተርታ ሰው፥ ወይም መልከ ጥፉ፥ ወይም በሽተኛ ፥ቢሆኑም የሚፈለግ የሚናፈቅ ነው። ሳያገቡ ለመኖር የወሰኑትም ቢሆኑ ፥ፍላጎቱ ያለው በአፍአ ሳይሆን በውስጥ ስለሆነ፥ ከኅሊና ውጣ ውረድ ሊድኑ አይችሉም። ስለሆነም ከኅሊናቸውና ከፍላጎታቸው ጋር እየታገሉ በገድል ይኖራሉ። በዚህ ትግል ማሸነፍም መሸነፍም ሊኖር ይችላል። የትዳር ጓደኛ ከውጭ ወደ ውስጥ የምናስገባው ሳይሆን፥ ከውስጣችን ፈልገን የምናገኘው ነው። ይህም ማለት፡- በአዳምና ሔዋን ሕይወት እንዳየነው፡- እግዚአብሔር የትዳር ጓደኞቻችንን አስቀድሞ በእያንዳንዳችን ሕይወት ውስጥ አስቀምጧቸዋል። በመሆኑም አንድ ሰው ሥዕል (ፎቶ ግራፍ) ይዞ የሥዕሉን ባለቤት እንደሚፈልግ በውስጣችን የተቀመጠውን፥ የተሣለውን ይዘን መፈለግ ይገባል።

የሰው ልጅ በእምነቱም ሆነ በሌላው ነገር ሁሉ ፍጹምነት ስለሌለው በፍለጋው (በመንገዱ) አጋዥ ያስፈልገዋል። ያንንም የሚሰጠን ያለ ጥርጥር እግዚአብሔር ነው። ለዚሀም የጾምና የጸሎት ሰው መሆን ያስፈልጋል። የነቢያት አለቃ ሙሴ ጽላቱን ከእግዚአብሰሔር እጅ የተቀበለው አርባ መዓልትና አርባ ሌሊት ጾሞ ነው፥ እንጀራ አልበላም፥ ውኃም አልጠጣም። ዘጸ ፴፩፥፲፰። እኛም እንደ ጽላት እንደ ታቦት ተከብረው የሚያስከብሩ የትዳር ጓደኞቻችንን በጾምና በጸሎት ልናገኛቸው እንችላለን ብለን ልናምን ይገባል። በአገራችን፡-«አቶ እገሌ እኮ ታቦት ማለት ናቸው፥ ወ/ሮ እገሊት እኮ ታቦት ማለት ናቸው፤» የሚባሉ ነበሩ። ታቦት የሚያሰኛቸው የጸና ሃይማኖታቸው፥ የቀና ምግባራቸው ነበረ።

ትምህርተ ጋብቻ ክፍል ፦ ፩

    ከ መልአከ ሰላም ቀሲስ ደጀኔ ሺፈራው ብሎግ የተወሰደ
http://www.betedejene.org/2010/12/blog-post.html
፩፦ « መጋባት በሁሉ ዘንድ ክቡር ነው፤» ዕብ ፲፫፥፬
          ጋብቻን ባርኮና ቀድሶ ለሰው ልጅ የሰጠው እግዚአብሔር ነው። በመሆኑም ጋብቻ የእግዚአብሔር ጸጋ ነው። ስለዚህ በዓይን ምኞት ተጋርደው፥ በሥጋ ፍላጐት ተነድተው ፥ በስሜት ፈረስ ጋልበው ፥ የሚገቡበት ሳይሆን ፦ በጸሎት እና በምልጃ ፈቃደ እግዚአብሔርን ጠይቀው የሚፈጽሙት ታላቅ ምሥጢር ነው።
          ጋብቻ የሰው ሁሉ ሕልም ነው። የማይመኘው፥የማይፈልገው የለም። የሰው  ሁሉ ጸሎት፥ የሰው ሁሉ ስእለት ነው። ለመሆኑ፦ ህልሙ የተፈታለት ፥ ጸሎቱ የደረሰለት ፥ ስዕለቱ የሰመረለት ስንቱ ይሆን? ያላገባው ይናፍቃል ፥ ያገባው ደግሞ ያማርራል። ከጋብቻ በፊት « መልአክ » የተባለ የትዳር ጓደኛ ከጋብቻ በኋላ «ሰይጣን» ይባላል። «እኔ የመረጥኩትን ካላገባሁ እሰቀላለሁ፤» እንዳልተባለ «ካልተፋታሁ መርዝ እጠጣለሁ፤» ለማለት ችግር የለም። ከጋብቻ በፊት ምክር ላለመስማት አሳብ ላለመቀበል፦ «ስለ እኔ ማንም አያገባውም፤» ተብሎ በር እንዳልተዘጋ ሁሉ ከጋብቻ በኋላ ግን ጣልቃ የማያስገቡት ሰው  የለም ፤ «ምን በወጣህ ፥ ምን በወጣሽ፤» የሚለውን ፈጥኖ ለመቀበል በሩ ለሁሉም ክፍት ነው።
፪፦ ጋብቻ እንዴት ተጀመረ?

          ጋብቻ በአዳምና በሔዋን እንደተጀመረ የጎላ፥ የተረዳ ፥ የታወቀ ነገር ነው። «ተባዕተ ወአንስተ ገብሮሙ፤ ወንድና ሴት አድርጎ ፈጠራቸው፤ » እንዲል፦ አዳም ሲፈጠር ሔዋን በውስጡ ነበረች። ዘፍ ፩፥፳፰። ይህም በባህርዩ ነበረች ማለት ነው። አንድ አካል፥ አንድ ሥጋ ከሚያሰኛቸው ምሥጢር አንዱና ዋነኛውም ይኸው ነው።
          ጋብቻ የተጀመረው በአዳም ጥያቄ ነው፤ ጥያቄዎም የኅሊና ማለትም ውሳጣዊ ነበር። ምክንያቱም፦ ከላይ እንደተ መለከትነው፦ የትዳር ጓደኛው በውስጡ ስለነበረች ነው። « እግዚአብሔር አምላክም፦ ሰው ብቻውን ይሆን ዘንድ መልካም አይደለም፤ የሚመቸውን ረዳት እንፍጠርለት፥አለ፤»ይላል። እግዚአብሔር እንዲህ ማለቱ፦ በአዳም ኅሊና ውስጥ ይህ ጥያቄ እንደሚነሣ ስለሚያውቅ ነው። መናገሩም ለአዳም ኅሊና እንጂ ፥ ሔዋን ለአዳም እንደምትፈጠርለት አስቀድሞ በእግዚአብ ሔር ዘንድ የተወሰነ ነው።