ጥቅስ

ጌታዬ
እግዚአብሔር ሆይ
እስከዚህ ያደረስኸኝ
እኔ ማን ነኝ ?
ቤቴስ ምንድር ነው?
2 ሳሙ 7፥18

Sunday 29 September 2013

አቡነ አኖሬዎስ ዘደብረ ጽጋጋ

አቡነ አኖሬዎስ ዘደብረ ጽጋጋ አትም ኢሜይል
መስከረም 13 ቀን 2005 ዓ.ም.

በመ/ር ሳሙኤል ተስፋዬ

anoros gedam 5.jpgአቡነ አኖሬዎስ በ13ኛው መ.ክ.ዘ የነበሩ ኢትዮጵያዊ ጻድቅ ናቸው፡፡ ትልቁ አኖሬዎስ ይሏቸዋል፡፡ የአቡነ ዜና ማርቆስ የእኅት ልጅ ናቸው፡፡ አባታቸው ቄስ ሰላማ እናታቸው ክርስቶስ ዘመዳ ሲባሉ የትውልድ ቦታቸው ምዕራብ ሸዋ ሙገር አካባቢ ልዩ ስሙ ማትጌ በሚባል ቦታ ነው፡፡ ገድለ ዜና ማርቆስ አባቱ ዘርዐ አብርሃም የተባለ የአቡነ ተክለ ሃይማኖት አባት ዘመድ ነበረ ይላል፡፡

ለአቡነ አኖሬዎስ ወላጆቻቸው ያወጡላቸው ስም ናርዶስ ሲሆን በሕፃንነታቸው የዳዊትን ንባብና የመጻሕፍትን ትርጓሜ ከተማሩ በኋላ በወቅቱ ከነበሩበት ግብፃዊ ጳጳስ ዲቁና ተቀበሉ፡፡ በወቅቱ ሐራንኪስ የተባለ የትርጓሜ መጻሕፍትና የዜማ ዐዋቂ በቤታቸው በእንግድነት ለብዙ ጊዜ በቆየበት ወቅት ለአቡነ አኖሬዎስ ዜማና ትርጓሜ መጻሕፍት በሚገባ አስተምሯቸዋል፡፡ በዚህም ምስጢራተ ቤተ ክርስቲያን፣ ዜማና ትርጓሜ መጻሕፍት የበለጠ ለመረዳት ከነበራቸው ፍላጎት አንጻር ወደ ደብረ አስቦ (ደብረሊባኖስ) በመሔድ ከአቡነ ተክለ ሃይማኖት ጋር ተገናኙ፡፡ በደብረ አስቦ (ደብረሊባኖስ) በገዳም ለረዥም ዓመታት ካገለገሉና ከተማሩ በኋላ በአቡነ ተክለ ሃይማኖት እጅ መንኩሰው አባ አኖሬዎስ ተባሉ፡፡

የገዳሙ መነኮሳት በሊቀ ዲያቆንነት መርጠዋቸው ትርጓሜ መጻሕፍትና ዜማ ያስተምሯቸው ነበር፡፡  ትጋታቸውን ያዩት የገዳሙ መነኮሳትም ከአቡነ ተክለ ሃይማኖት በታች የገዳሙ መጋቢ አድረገው መረጧቸው፡፡ በዚያ ዘመን በገዳሙ ወንዶች እና ሴቶች መነኮሳዪያት በአንድነት ይኖሩ ነበር፡፡ ነገር ግን አቡነ አኖሬዎስ አቡነ ተክለ ሃይማኖትን አማክረው የሴትና የወንድ ገዳም እንዲለይ አደረጉ፡፡ ከዚህ በኋላ በወቅቱ በነበሩት አቡነ ቄርሎስ ዘንድ ተልከው ቅስናን ተቀበሉ፡፡