እግዚአብሔር አባታችን የሚረባንን የሚጠቅመንን እያስተማረን በመንገዳችን ሁሉ እየመራን ረዥሙን ጉዞ አንድ ብለን ጀምረን ይኸው አራተኛው ምዕራፍ ላይ ደረስን አሁንም በቃሉ ምግብነት የተራበችዋን ነፍሳችንን እንዲመግብልን የተቀደሰ ፍቃዱ ይሁን፤ እንደምናስታውሰው በክፍል አንድ የምሥጢረ ተክሊል ምንነትን፤ በክፍል ሁለት የጋብቻ ዓላማን? እንዲሁም በክፍል ሦስት ቅድመ ጋብቻን ጀምረን እንዳይበዛ በማሰብ ይቀጥላል ብለን ማቆማችንን ከወዲሁ ላስታወሳችሁ እወዳለሁ፡፡
ዛሬም እንደ እግዚአብሔር ፍቃድ በክፍል አራት ትምህርታችን የጀመርነውን የቅድመ ጋብቻን ትምህርት እናጠቃልልና ድንግልና እና ተክሊል በሚል ርዕስ ደግሞ በክፍል አምስት እርሱ እንደፈቀደ እንማማራለን፤ እግዚአብሔር ከሁላችን ጋር ይሁን፡፡አሜን
ወዳጆቼ የቀድሞዎቹ ነገስታቶች ክርስትናቸውን አጥብቀው ይይዙ የነበሩ በመሆኑ ይተዳደሩበት የነበረውን መጽሐፍ ፍትሐ ነገስት ማለታቸውን መቅድሙ ይገልፃል፡፡ ይህ መጽሐፍ ለሀገራችንም ሆነ ለዓለም ሕዝብ የሕግ ምንጭ ሆኖ አሁን ደረስ የሚያገለግል ታላቅ መጽሐፍ ነው፡፡ ከአረበኛ ወደ ግእዝ ቀጥሎም በእንግሊዝኛ እንዲሁም በ1962 ዓ.ም በግእዝ እና በአማረኛ የታተመው መጽሐፍ አገልግሎቱን የዋለው ከ15ኛው መቶ ክፍለ ዘመን(ዓፄ ዘርአያዕቆብ 1444-1468) ጀምሮ ሲሆን የኢትዮጵያ ሕገ መንግስት እስከ ረቀቀበት(1948 ዓ.ም) ድረስ በዚህ የሕግ መጽሐፍ ኢትዮጵያ ትተዳደርበት እንደነበረ የታሪክ ሕያው ምስክርነትን መጥቀስ ይቻላል፡፡
ወዳጆቼ ቅድመ ጋብቻ ላይ (በምንተጫጭበት ወቅት) ብዙ ጊዜ የማናስተውላቸው እና ከገባንበት በኋላ የምንነቀባቸው ስህተቶች አሉ፡፡