ጥቅስ

ጌታዬ
እግዚአብሔር ሆይ
እስከዚህ ያደረስኸኝ
እኔ ማን ነኝ ?
ቤቴስ ምንድር ነው?
2 ሳሙ 7፥18

Friday, 22 February 2013

ጾመ ነነዌ

ጾመ ነነዌ




እግዚአብሔር ነብዩ ዮናስን ወደ ነነዌ ምድር በኃጢአታቸው ምክንያት ሊያመጣው ካሰበው የእሳት ዝናም እንዲትርፉ ቢልከው እግዚአብሔርን ቸርነት ስለሚያውቀው ቸርነትህ ከልክላህ ሳታጠፋቸው ብትቀር እኔ የሐሰት ነቢይ እባል የለምን? ብሎ ሰግቶ ወደ ተርሴስ ሃገር ከነጋዴዎች ጋር ተሳፈረ።
እግዚአብሔርም ታላቅ ማዕበልን አስነሳ በመርከቧ ያሉ ሰዎችም እርስ በራሳቸው ዕጣን ተጣጥለው በዮናስ ላይ ወደቀ። እርሱም ያደረገውን ሰለሚያውቅ ሌሎቹ በውሰጥ ያሉት እንዳይጣል ብዙ ጥረት ቢያደርጉም የግድ መጣል ስለ ነበረበት ወደ ባሕር ተጣለ። እግዚአብሔርም ታላቅ ዓሣ አንበሪን አዘጋጅቶ በከርሠ ዓሣ አንበሪ ሦስት መዓልት ሦስት ሌሊት ቆይቶ በሦስተኛው ቀን በአንጻረ ነነዌ ተፍቶታል። በግድም ቢሆን ስለ ሚመጣባቸው መዓት አስተምሯል። ትንቢተ ዮናስ ምዕራፍ 1 እና 2 ነብዩ ዮናስ ለመጀመርያ ጊዜ ወደ አሕዛብ ሀገር የተላከ ነቢይ ነው።

ዮናስ ማለት ርግብ ማለት ነው። ርግብ የዋህ እንደሆነች እሱም የዋህ ነውና ይህ ቅጽል ተቀጽሎለታል። የርግብ የዋህነት እንደምን ነው ቢሉ በማየ አይኅ (በጥፋት ውሃ )ጊዜ በእባብ አፍ ውስጥ እንቁላል ጥላለች።

Tuesday, 12 February 2013

እንጦንዮስ አበ መነኰሳት

እንጦንዮስ አበ መነኰሳት አትም ኢሜይል

ጥር 22 ቀን 2005 ዓ.ም.
  • ምንጭ፡- የበረሃው ኮከብ ቅዱስ እንጦንዮስ መጽሐፍ
ጨለማ በዋጠው በግብፅ በረሃ ውስጥ ለብዙዎች አርዓያ በሆነ የእምነት ገድል የቅድስናን ብርሃን በማብራቱ የበረሃው ኮከብ ብለው ብዙዎች ይጠሩታል፡፡

kiduse entonseብፁዐዊ ቅዱስ እንጦንስ በምንኩስና ሕይወት ለመኖር ከጌታችን ከመድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተማረው አብነታዊ ትምህርት (ማቴ.4፥1-10) ከዚህ ዓለም ተድላና ደስታ በመራቅ ከሰዎች ሁሉ ተለይቶ ፍጹም መንፈሳዊ ተጋድሎን በመጋደል በተወለደ በ106 ዓመቱ ጥር 22 ቀን በ356 ዓ.ም. ከዚች ዓለም በሥጋ ተለይቷል፡፡ “ክቡር ሞቱ ለፃድቅ በቅድመ እግዚአብሔር” “የፃድቅ ሰው ሞቱ በእግዚአብሔር ፊት የከበረ ነው” በማለት ክቡር ዳዊት እንደተናገረው፣ “ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የቅዱሳን የልደታቸውን ጊዜ፣ የተጋድሏቸውን ሁናቴ፣ ቃል ኪዳን የተቀበሉባቸውንና ያረፉባቸውን ዕለታት በክብር ታስባለች፡፡ ይህም በቅዱስ መጽሐፋችን “የፃድቅ መታሰቢያ ለበረከት ነው”(ምሳ.10÷7)፡፡ በመሆኑም “ስለ ፅድቅ የሚሰደዱ ብጹአን ናቸው ÷ መንግሥተ ሰማያት የእነርሱ ናትና” (ማቴ.5÷8) በሚለው በጌታችን ትምህርት የዚችን ዓለም ጣዕም ንቆ በምናኔ በመኖር ለመነኮሳት አብነት የሚሆናቸውን የቅዱስ እንጦንስን ዜና ሕይወት አቅርበናል፡፡ለመሆኑ ቅዱስ እንጦንስ ማን ነው? አስተዳደጉና የፈጸማቸው አገልግሎቶቹ ምን ይመስላሉ?

ልጅነት
እንጦንዮስ/እንጦንስ/ ትውልዱ ግብጻዊ ሲሆን ቤተሰቦቹም መልካሞችና ባለጸጎች ነበሩ፡፡ እነርሱም በሕፃንነት ኑሮው ከቤቱና ከወላጆቹ በስተቀር ምንም አላወቀም፡፡ እያደገና ዕድሜው እየጨመረ ሲሄድ ትምህርት ቤት አልገባም ነበር፡፡ ይህም ከሌሎች ልጆች ጋር ጓደኝነት ባለመፈለጉ ነበር፡፡

Thursday, 31 January 2013

ዕረፍታ ለእግዝእትነ ቅድስት ድንግል ማርያም (ጥር 21)


ማርያም ማለት መርሕ ለመንግሥተ ሰማያት ማለት ነው፡፡ ምዕመናንን እየመራች ወደ መንግስተ ሰማያት ታስገባለችና፡፡ አንድም ፍጽምት ማለት ነው፡፡ በሥጋም በልቦናም ንጽሕት ናትና፡፡ ማርያም ማለት ልዕልት ማለት ነው፡፡ ከፍጡራን በላይ ናትና፡፡ ‹‹ማር›› በምድር ‹‹ያም›› በሰማይ ናት፡፡ ማር በምድር ተወዳዳሪ የሌለው ምግብ ነው፡፡ ያም በሰማይ ቅዱሳን የሚመገቡት በብሔረ ሕያዋን በብሔረ ብፁዓን ያሉ ቅዱሳን የሚመገቡት ጣፋጭ ምግብ ነው፡፡ የእመቤታችን ርህራሄዋ በምድርም በሰማይም ሁሉ ጣፋጭ ነውና ማርያም ተባለች፡፡እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በዚህ ምድር ላይ 64 ዓመት ኖራ ጥር 21 እሑድ ቀን ጌታ እልፍ አእላፍ መላእክቱን አስከትሎ መጥቶ እናቴ ሆይ ከዚህ ዓለም ድካም ላሳርፍሽ መጣሁ ቢላት ልጄ ሰማይና ምድር የማይወስኑህን ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን በማኅፀኔ ተሸክሜ፣ በድንግልና ወልጄህ እሞታለሁን? አለችው፡፡ በሲኦል የሚሰቃዩ ነፍሳትን አሳይቶ እናቴ ሆይ ሞትሽ ለእኚህ ቤዛ ይሆናቸዋል አላት፡፡ እመቤታችንም እኚህን ከማርክልኝስ ይሁን አለችው፡፡ ቅድስት ሥጋዋንም ለይቶ በቃለ አቅርንት በዝማሬ መላእክት አሳረጓት፡፡

Wednesday, 23 January 2013

አቡነ ሐራ ድንግል

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሀዱ አምላክ አሜን::

ከሁሉ አስቀድመን የአንዲት ቅድስት ቤተ ክርስቲያንልጆች የሆን እኛ የክርስቶስ ወገኖች ሰዎች ነ...ገርን ከማብዛት በማሳነስ ነገርን ከማስረዘም በማሳጠር ክቡርና ልኡል ትሩፋቱ ፍፁም ገድሉም ብዙ የሆነ ምስራቃዊ የክብር ኮከብ አርያማዊ የፅድቅ ጸሀይ የኦርቶዶክሳዊ ሀይማኖት ዓምድ የመንፈሳዊ ምግባርማደሪያ የሆነየአባታችን ሐራ ድንግልን ገድሉንና ትሩፋቱን የፅድቁንም ስራ እንጽፍ ዘንድ ህይወትን ሰጪ በሚሆን በባታዊ አድሮ በሚኖር ገዳማዊውን በሚጎበኝ የአለማዊውንም ሰው በደል በመለኮታዊ ስልጣኑ በሚያስተሰርይ በአምላክ ፈቃድ ለመጀመር ተግተን ተመኘን::

ለሁላችንም የጥምቀት ልጆች ከኦሪታዊው ከሙሴና ከወንጌላዊው ከዮሀንስ ጋር አሸናፊ እግዚአብሄርን በቀናች ሀይማኖትና በመልካም ምግባር ካገለገሉት ከጻድቃንና ከመነኮሳትም ጋር ሰማያዊ የነፍስ ደስታ እድልን ያድለን ክብር ምስጋና ለእርሱ ይሁን ለዘላለሙ አሜን::

አቡነ ሐራ ድንግል

አስቀድመን በመጻፋችን የጠራነው የዚህ ጻድቅ አባቱና እናቱ በላጉና ምድር ይኖሩ ነበር :: እርስዋም ከደራ ምድር አንድ ክፍል ናት::

Friday, 18 January 2013

እውነት እውነት እልሀለሁ ሰው ከውሃና ከመንፈስ ካልተወለደ በቀር ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም።” ዮሐ ፫፡፭

“እውነት እውነት እልሀለሁ ሰው ከውሃና ከመንፈስ ካልተወለደ በቀር ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም።” ዮሐ ፫፡፭ አትም ኢሜይል

በይበልጣል ጋሹ
ጥር ፲ ቀን ፳፻፭ ዓ.ም.
timiket 2005ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመዋዕለ ስጋዌው በምድር በነበረበት ዘመን ከፈጸማቸው እና ለሰው ልጅ ከሰጣቸው ሚስጢራት አንዱ ጥምቀት ነው። “ጥምቀት” የሚለው ቃል አጥመቀ ከሚለው የግዕዝ ግሥ የተገኘ ሲሆን ትርጉሙም፣ መነከር፣ መዘፈቅ፣ መደፈቅ፣ መላ አካልን በውሃ ውስጥ ማስገባት ማለት ነዉ። በሚስጢራዊ ትርጉም ደግሞ ብዙ ምሳሌዎች አሉት። ከምሳሌዎች መካከልም፦ የአብርሃም ከሃገሩ መውጣትና ዮርዳኖስን ተሻግሮ ወደ ከነዓን መግባት የጥምቀት ምሳሌ ነው። ምዕመናን ከዓለመ ኃጢአት ወጥተው የመንግሥተ ሰማያት ዜጎች የሚሆኑት በጥምቀት ነውና። ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ በ፩ጴጥ ፫፡፳፩ ላይ ኖህ ከጥፋት ውሃ የዳነባትን መርከብ የጥምቀት ምሳሌ ናት ብሏታል ምክንያቱም ምዕመናን ከጥፋት የሚድኑት በጥምቀት ስለሆነ። እንዲሁም ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ በ፩ቆሮ ፲፡፩ እስራኤል ከግብፅ የባርነት ቀንበር ተላቀው የኤርትራን ባሕር ተሻግረው ወደ ምድረ ርስታቸው ያደረጉትን ጉዞ የጥምቀት ምሳሌ አድርጎ ተናግሯል፤ምእመናን ባሕረ ኃጢአትን ተሻግረው ምድረ ርስት መንግሥተ ሰማያት የሚወርሱት በጥምቀት ነውና። ጥምቀት ከእግዚአብሔር ዳግም የምንወለድበት፣የቤተ ክርስቲያን አባል የምንሆንበት፣ የኃጢያት ስርየት የስጋ ፈውስ የምናገኝበት ረቂቅ ምስጢር ነው።
1. የጥምቀት መስራቹ ማነው?
አግዚአብሔር ቀድሞ በነቢያት ያናገረውን ለመፈፀም ከቅድስት ድንግል ማርያም በኅቱም ድንግልና ተጸንሶ በኅቱም ድንግልና ተወለደ።ሉቃ ፪፡፩ ከኃጢአት በስተቀር እንደኛ ሰው ሆኖ ሕገ ጠባዕያዊን እና ሕገ መጽሐፋዊን እየፈጸመ ቀስ በቀስ አደገ። እንደዚህ እያለ ሠላሳ/30/ ዘመን ሲሞላው በዘመነ ሉቃስ በዕለተ ማክሰኞ ሌሊት 10 ሰዓት ጥር 11 ቀን በዮሐንስ እጅ ይጠመቅ ዘንድ ወደ ዮርዳኖስ ወንዝ ሄደ። ወደ ዮርዳኖስ ወንዝም ሄዶ ዮሐንስን አጥምቀኝ አለው። ዮሐንስም መልሶ እኔ ሎሌህ በአንተ በጌታዬ እጠመቅ ዘንድ ይገባኛል እንጂ አንተ በእኔ ትጠመቃለህን? አለው። ጌታችንም ሕግን ልንፈጽም ይገባናልና አጥምቀኝ አለው። ዮሐንስም በአብ ስም እንዳላጠምቅህ አብ በአንተ ህልውና ነው፣ በወልድ ስም እንዳላጠምቅህ ወልድ አንተ ነህ በማን ስም አጠምቅሀለው አለው? “ወልዱ ለአብ ከሣቴ ብርሀን ተሣሃለነ” ብርሃንን የምትገልጽ የአብ የባህርይ ልጅ ይቅር በለን እያልክ አጥምቀኝ አለው። ዮሐንስም ክርክሩን አቁሞ አጠመቀው። ማቴ ፫፡፲፫-፲፯ በዚህ መሠረት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በ30 ዘመኑ በዮሐንስ እጅ በዮርዳኖስ ወንዝ ተጠመቀ። የሠው ልጅ ሁሉ ይድን ዘንድ እና ዳግመኛ ከሥላሴ ይወለድ ዘንድ እርሱ ተጠምቆ ጥምቀትን ሰጠን። በመሆኑም የጥምቀትን ምስጢርና አስፈላጊነት ያስተማረ፤ ጥምቀትንም የመሰረተው እርሱ እራሱ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ከዚያም “ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አጥምቁ” በማለት ለሐዋርያት ሥልጣንና ትዕዛዝ ሰጥቷል። ማቴ ፳፰፡፲፱
2. አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለምን ተጠመቀ፤
እግዚአብሔር አምላክ የሰውን ልጅ መጥፋት ተመልክቶ አዳምን ያድነው ዘንድ ወደደ እንደኛ ሰው ሆኖ ተወለደና አደገ። አዳምን ሲፈጥረው የ30 ዓመት ወጣት አድርጎ ነበርና ያጣኃውን ልጅነት እኔ በ30 ዘመኔ ተጠምቄ በጥምቀት እመልስልሃለሁ ሲለው በ30 ዘመኑ በዮርዳኖስ ወንዝ ተጠመቀ። ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የምታስተምራቸዉን የጌታችን ጥምቀት ምክንያቶች እንደሚከተለው እናያለን፦
ሀ) አርዓያ ለመሆን
እርሱ በዮሃንስ እጅ ተጠምቆ እናንተም እንደዚህ ብትጠመቁ ልጅነትን ወይም ከሥላሴ መወለድን ታገኛላችሁ ለማለት ነው። እሱማ እፀድቅ አይል ጻድቅ፣ እከብር አይል ክቡር፣ እነግስ አይል ንጉሥ ነውና ለእኛ አርያ ለመሆን ብሎ ተጠመቀ እንጂ።
ለ) ሚስጢረ ሥላሴን ለማስረዳት
በመጽሐፍ ቅዱስ በተለያየ ቦታ ላይ የተገለጸዉ የእግዚአብሔር አንድነት ሦስትነት በጥምቀት ጊዜም ሰው በሚረዳው መጠን ተገልጧል። ይህም እግዚአብሐር አብ በደመና ሆኖ “በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው” እያለ ለወልድ ሲመሰክር፤ እግዚአብሐር ወልድ በዮርዳኖስ ወንዝ በዮሐንስ እጅ ሲጠመቅ፤ መንፈስቅዱስ በርግብ አምሳል በወልድ ላይ ሲወርድ፤ ሚስጢረ ሥላሴ ወይም የእግዚአብሐር ሦስትነት ማለትም አብ፣ ወልድ፣ መንፈስ ቅዱስ ለሰዉ በሚረዳዉ መልኩ ተገለጠ። ማቴ ፫፡፲፫-፲፯
ሐ) ትንቢቱንና ምሳሌውን ለመፈፀም
እግዚአብሔር አምላክ የተናገረውን እና በነቢያት ያናገረውን አያስቀርምና ቃሉን ለመፈፀም በዮርዳኖስ ተጠመቀ። ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ “አቤቱ ውሆች አዩህ፡ ውሆችም አይተውህ ፈሩ ፡ጥልቆች ተናወጡ ውሆችም ጮሁ” መዝ ፸፮፡፲፮ እንዲሁም ነብዩ ሕዝቅኤል እንደተናገረው “ጥሩ ውሃንም እረጭባችኋለሁ እናንተም ትጠራላችሁ ከርኩሰታችሁም ሁሉ አጠራችኋለሁ አዲስ መንፈስ በውስጣችሁ አኖራለው” ሕዝ ፴፮፡፳፭ ብሎ በነቢያት ያናገረውን ለመፈፀም በዮርዳኖስ ወንዝ ተጠመቀ።
3 ዮርዳኖስ ወንዝንስ ለምን መረጠ
በዮርዳኖስ ወንዝ የተጠመቀበት ምክንያትም እንደሚከተለው እናያለን፦
v ለዮርዳኖስ የተነገረውን ትንቢት ለመፈፀም በዮርዳኖስ መጠመቅ አስፈለገው። ትንቢቱም “አንቺ ባሕር የሸሸሽ፡ አንቺም ዮርዳኖስ ወደ ኋላሽ የተመለሽ ምን ሁናችኋል?” መዝ ፻፲፫፡፭ በማለት ስለ ዮርዳኖስ የተነገረውን ትንቢት ለመፈፀም በዮርዳኖስ ተጠመቀ።
v ምሳሌውን አማናዊ ለማድረግ፤ ዮርዳኖስ ምንጩ አንድ ነው፣ ዝቅ ብሎ ግን በደሴት ይከፈላል፣ ከታች ወርዶ ይገናኛል። ዮርዳኖስ ከላይ ምንጩ አንድ እንደሆነ የሰው ሁሉ ምንጩ አንድ አዳም መሆኑን፣ ዝቅ ብሎ በደሴት መከፈሉ እስራኤል በግዝረት አሕዛብ በቁልፈት የመለየታቸው፣ ከታች ወርዶ መገናኘቱ እና ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመገናኛው ላይ መጠመቁ ሕዝብና አሕዛብን በጥምቀት አንድ ሊያደርግ መምጣቱን ያጠይቃል። እንዲሁም አባታችን ኢዮብ ከደዌው የዳነው በዮርዳኖስ ወንዝ ተጠምቆ ነው። ኢዮብ የአዳም ምሳሌ ነው፤ ደዌው የመርገመ ሥጋ የመርገመ ነፍስ ምሳሌ ነው፤ ዮርዳኖስ የጥምቀት ምሳሌ ነው። የአዳም ዘር ከማኅፀነ ዮርዳኖስ በጥምቀት ዳግም ተወልዶ ከመርገመ ሥጋ ከመርገመ ነፍስ ይላቀቃል ብሎ በዮርዳኖስ ተጠመቀ። ኤልያስ ዮርዳኖስን ተሻግሮ ወደ ብሔረ ሕያዋን አርጓል። ምዕመናንም አምነው ተጠምቀው ገነት መንግስተ ሰማያት የመግባታቸውን ምሳሌ ለማስረዳት አምላካችን በዮርዳኖስ ተጠመቀ።
v የእዳ ደብዳቤያችንን ይደመስስልን ዘንድ፦ ዲያብሎስ የጨለማ መጋረጃ ጋርዶ በአባታችን አዳም እና በእናታችን ሔዋን ስቃይ መከራ አፀናባቸው ስመ ብኩርናችሁን ጽፋችሁ ብትሠጡኝ ፍዳውን አቀልላችኋለሁ አላቸው። እነሱም ስቃዩ እና መከራው የቀለለላቸው መስሏቸው “አዳም ገብሩ ለዲያብሎስ ፤ ሔዋን ዓመቱ ለዲያብሎስ” አዳም የዲያብሎስ ባርያ ሔዋን የዲያቢሎስ ገረድ ብለዉ ጽፈዉ ሰጡት። እሱም በሁለት ገጽ አድርጎ አንዱን በሲኦል አንዱን በዮርዳኖስ አስቀመጠው። ከአምላካችን የሚሰወር ነገር የለምና በዮርዳኖስ የጣለውን ጌታችን በጥምቀቱ ጊዜ እንደሰውነቱ ረግጦ እንደአምላክነቱ አቅልጦ ለማጥፋት ሲል በዮርዳኖስ ተጠመቀ። በሲኦል ያስቀመጠውን ጌታችን በዕለተ ዓርብ በአካለ ነፍስ ወርዶ ነፍሳትን ሲያወጣ በመለኮታዊ ጥበቡ አጥፍቶላቸዋል።
ወነዓምን በአሃቲ ጥምቀት
አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለአይሁድ መምህር ለኒቆዲሞስ “እውነት እውነት እልሀለሁ ሰው ከውሃና ከመንፈስ ካልተወለደ በቀር ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም።” በማለት ዳግም ልደት ከውሃና ከመንፈስ የሚገኝ መሆኑን እና የጥምቀትን አስፈላጊነት በሚገባ አስረድቶታል። እኛም ዛሬ ይህንን አምላካዊ ቃል መሠረት አድርገን ጌታ በዕለተ ዓርብ ስለኛ በተሰቀለ ጊዜ በፈሰሰው ማየ ገቦ እንጠመቃለን ስንጠመቅም ወንዶች አዳም ተፈጥሮ ገነት በገባበት በ40ኛው ቀን ሴቶች ሔዋን ተፈጥራ ገነት በገባችበት በ80ኛው ቀን ቤተ ክርስቲያን ሥርዓተ ጥምቀትን በመፈጸም የመንፈስ ቅዱስ ልጅነትን ታሰጠናለች/ ኩፋሌ ፬፡፱/። ከዚህም ሌላ ወንድ የወለዱ በአርባ/40/ ሴት የወለዱ በሰማንያ/80/ ቀን ሕፃኑን ወደ ቤተ መቅደስ ማቅረብ እንዳለባቸው ታዝዟል/ዘሌ ፲፪፡፩-፰/ ውንድ የወለዱ ሴቶች ከደመ ሕርስ የሚነጹት ባርባ፤ ሴት የወለዱ ደግም በሰማንያ ቀን ነውና ። ይህ በብሉይ ኪዳን የነበረው ሥርዓት በአርባ ቀን በሰማንያ ቀን ለሚደረገው የክርስቲያን ልጆች ጥምቀት ምሳሌ ነው። ሕፃናቱ ወደ እግዚአብሔር ፊት መቅረብ የሚጀምሩት በዚህ ቀን ነውና ። እዚህ ላይ በእምነት የተለዩን ወገኖቻችን በህጻናትጥምቀት ላይ ጥያቄ ያነሳሉ። ቤተ ክርስቲያናችን ግን መጽሐፍ ቅዱሳዊ መልስ ሰጥታ ትክክለኛነቱን ታረጋግጣለች። “ህፃናት ወደ እኔ ይመጡ ዘንድ ተዋቸው አትከልክሏቸው መንግስተ ሰማያት እንደእነርሱ ላለች ናትና” ማቴ ፲፱፡፲፬ ብሎ አምላካችን በመዋዕለ ስብከቱ ሕፃናቱን ባርኮ በማነኛውም የቤተ ክርስቲያን በረከት ተካፋይ መሆን እንዳለባቸው ለሐዋርያትና ለምእመኑ በሚገባ አስተምሯል። እስኪ አንድ መጻፍቅዱሳዊ እና የጥምቀት ምሳሌ የሆነውን ግዝረትን እናንሳ አብርሃም በእግዚአብሔር ባመነ ጊዜ ሽማግሌ ነበር። ነገር ግን ለማመኑ ምልክት እንዲሆነው ተገዘር ተባለ ተገዘረ። ከዚህ በኋላ የአብርሃም ዘሮች የሆኑ ሁሉ በስምንተኛ ቀናቸው የሚገዘሩት የአብርሃም ልጆች ስለሆኑ ነው። ታድያ እንደ አብርሃም ሳያምኑ ሕፃናት ለምን ተገዘሩ??? በቤተ ክርስቲያንም ሕፃናት የሚጠመቁት ከክርስትያን ቤተሰብ ስለተወለዱ ነው። ጌታችንም በወንጌሉ ሂዱና በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው አሕዛብን ሁሉ አስተምሩ ያዘዝኋችሁንም እንዲጠብቁ አስተምሩአቸው። ባለው መሰረት ቤተ ክርስቲያናችን ለህጻናት ጥምቀትን አስቀድማ ታስተምራለች። ማቴ ፳፰፡፲፱
“ወነአምን በአሐቲ ጥምቀት ለስርየተ ኃጢአት” ኃጢአት በሚሰረይባት በአንዲት ጥምቀት እናምናለን ተብሎ በጸሎተ ሃይማኖት ላይ አባቶቻችን በደነገጉልን መሰረት በጥምቀት ከአብራከ መንፈስ ቅዱስ ዳግም ልደትን እንደምናገኝ እና የኃጢአት ስርየትም እንደሚገኝ ያስረዳናል። “አሁን ለምን ትዘገያለህ ተነሳና ስሙን እየጠራህ ተጠመቅ ከኃጢአትህም ታጠብ” ሐዋ ፳፪፡፲፩ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ኃጢአቱ የተወገደለት የእግዚአብሔር አገልጋይ እንዲሆን በተጠራ ጊዜ ሳይሆን በተጠመቀ ጊዜ ነው። ከዚህ ላይ የምንረዳው በጥምቀት ኃጢአታችን እንደሚሰረይልን አምነን ከመከራ ስጋ ከመከራ ነፍስ መዳን የምንችልበት መሆኑና በጥምቀት ኃጢአታችንን አስወግደን ከእግዚአብሔር ጋር ህብረት ይኖረናል ከእርሱም ጋር እንሞታለን ከእርሱም ጋር እንነሳለን።ለዚህም ነው ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ጥምቀትን በሞትና በመቃብር መስሎ ያስተማረን/ሮሜ ፮፡፫/ በሞት ጊዜ ነፍስና ስጋ እንደሚለያዩ በጥምቀትም አሮጌው ሰውነት ይሞታል ይቀበራል አዲሱ ሰውነት አዲስ ሕልውና ህይወት ይጀምራል። ማንኛውም ክርስቲያን በማንኛውም ነገር ክርስቶስን ሊመስል ይገባዋል። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “እኔን ምስሉ” ብሏልና ሞቱን በሚመስል ሞት ከእርሱ ጋር ከተባበርን ትንሳኤውን በሚመስል ትንሳኤ ደግሞ ከእርሱ ጋር እንተባበራለን። ከክርስቶስ ጋር የምንሞተውና የምንቀበረው ደግሞ በጥምቀት ነው።
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለሰው ልጅ ድኅነት ከዮሐንስ እጅ ይጠመቅ ዘንድ ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ ያደረገውን አምላካዊ ጉዞ ለማሰብ በየአመቱ ጥር 10 ቀን ታቦታቱ በካህናትና በምእመናን ታጅበው ወደ ባህረ ጥምቀት በመጓዝ አምሳለ ዮርዳኖስ በሆነውና በተዘጋጀላቸው ቦታ በክብር ያርፋሉ። ሌሊቱን በሙሉ በማኅሌትና በቅዳሴ በዓሉ እየተከበረ ያድራል። ጧት ጥር 11 ቀን የበረከት ጥምቀት ከተፈፀመ በኋላ በደማቅና በልዩ ሥነ ሥርዓት በስብሐተ እግዚአብሔር በዓሉ ይከበራል። ታቦታቱም በማህሌት፣ በመዝሙርና በእልልታ ታጅበው ወደ መንበራቸው በክብር ይመለሳሉ። ይህ ዕለት ከባርነት ነጻ የወጣንበት፣ የእዳ ደብዳቤያችን የተደመሰሰበት፣ ከእግዚአብሔር ጋር አንድ የሆንበት ስለሆነ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን የጥምቀትን ሥርዓትና ምስጢር ለዘመናት ስትፈፅም ዛሬም እየፈፀመች ወደፊትም በመፈፀም ትኖራለች። ምክንያቱም ከላይ በትምህርታችን እንዳየነው ለሰው ልጅ የድኅነት በሩ ዳግም በጥምቀት ከአብራከ መንፈስ ቅዱስ መወለድ ነው ከዚህ ውጪ የእግዚአብሔርን መንግሥት መውረስ አይቻልምና።
እኛም የአዳም ልጆች ይህን የቤተ ክርስቲያን ሥርዓትና ህግ የማስጠበቅ ግዴታና ኃላፊነት እንዳለብን ተገንዝበን በ40 እና በ80 ቀን ያገኘነውን የእግዚአብሔር ልጅነት አዳምን ያሳተ ዲያብሎስ ልጅነታችንን እንዳይነጥቅብን አጥብቀን መያዝ ይገባናል። ሌሎች ወገኖቻችንም የዚህ ታላቅ ጸጋ ተጠቃሚ እንዲሆኑ ማድረግ እንድንችል የእግዚአብሔር መልካም ፈቃድ ይሆንልን። ለዚህም በጾምና በጸሎት እንድንተጋ አምላከ ቅዱሳን ልዑል እግዚአብሔር ይርዳን። በዓሉን የሰላም፣የፍቅር፣ የአንድነት፣ የመተሳሰብና የበረከት ያድርግልን። አሜን። ወስብሐት ለእግዚአብሔር።+++
1. የጥምቀት መስራቹ ማነው?
አግዚአብሔር ቀድሞ በነቢያት ያናገረውን ለመፈፀም ከቅድስት ድንግል ማርያም በኅቱም ድንግልና ተጸንሶ በኅቱም ድንግልና ተወለደ።ሉቃ ፪፡፩ ከኃጢአት በስተቀር እንደኛ ሰው ሆኖ ሕገ ጠባዕያዊን እና ሕገ መጽሐፋዊን እየፈጸመ ቀስ በቀስ አደገ።

Thursday, 10 January 2013

ቅድስት ወለተ ጴጥሮስ አትም ኢሜይል

አባቷ ባሕር አሰግድ እናቷ ደግሞ ክርስቶስ አዕበያ ይባላሉ። ትውልዷ ከዳሮ /ምስራቅ ኢትዮጵያ/ ወገን ነው። ወንድሞቿ ዮሐንስና ዘድንግል በንጉሥ ሱስንዮስ ጊዜ ታላላቅ ባለስልጣናት ነበሩ። እናት አባቷ በህግ በስርዓት ካሳደጓት በኋላ ሥዕለ ክርስቶስ የሚባል የስስኑዮስ የጦር አበጋዝ ቢትወደድ አግብታ 3 ልጆች መውለድዋን ገድሏ ይናገራል። ይህ ቢትወደድ ይኖርበት የነበረው ግንብ ቤት ፍራሽ እስከ አሁን ድረስ በጋይንት ስማዳ ይታያል።
ወለተ ጴጥሮስ ከቢትወደድ ሥዕለ ክርስቶስ ጋር በሰላም በመኖር ላይ እያለች ንጉሡ አጼ ሱስንዮስ የተዋሕዶ ሃይማኖቱን ቀይሮ በሮማውያን ሀሰተኛ መምህራን በመታለል ካቶሊክነትን ተቀብሎ የኢትዮጵያ ህዝብም ካቶሊክ እንዲሆን ዐወጀ። በዚህ ዐዋጅ የተነሣ በንጉሡ ደጋፊዎችና የቀደመ ሃይማኖታችንን አንለቅም ባሉት እውነተኛ የተዋህዶ ምዕመናን መካከል ታላቅ ጠብ ሆነ።